group-telegram.com/tikvahethiopia/93045
Last Update:
" ከታህሳስ 2 እስከ ታህሳስ 5 ቀን 2017 ዓ/ም ብቻ 6 ሹፌሮች ከነረዳታቸው በታጣቂዎች ተገድለዋል " - ጣና የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ማኅበር
🚨 " ሹፌርን ማገት የስራ ዘርፍ ሆኖ እየተኖረበት ነው !! "
የከባድ መኪና ሹፌሮች በሃገር አቋራጭ እና ከተማ አቋራጭ ጉዞዎቻቸው ወቅት በታጣቂዎች የሚደርስባቸው እገታ እና ግድያ ተባብሶ መቀጠሉን ጣና የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ማኅበር ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አስታውቋል።
ባለፉት 5 አመታት በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተገደሉ ሹፌሮች ቁጥርም 230 መሻገሩን ስሜ አይጠቀስ ያሉ የማህበሩ አመራር ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።
ከታህሳስ 2 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ/ም ብቻ ስድስት ሹፌሮች ከነረዳታቸው በታጣቂዎች ተገድለዋል ብለዋል።
አራቱ ሹፌሬች የተገደሉት በመተማ ጎንደር መንገድ ጭልጋ አካባቢ ሲሆን ሁለቱ ደግሞ ከጎንደር ሳንጃ መንገድ ፈረስ መግሪያ አካባቢ ነው።
ፈረስ መግሪያ አካባቢ የተገደሉት ሹፌርና ረዳት ሲሆኑ ከታህሳስ 2 ጀምሮ አግተው ገንዘብ እንዲሰጣቸው ሲደራደሩ ቆይተው ታህሳስ 5/2017 ዓ/ም 120 ሺ ብር ከተቀበሉ በኋላ ገድለው እንደጧላቸው ሃላፊው አስረድተዋል።
የችግሩን ክብደት ሲያስረዱም " አንዳንድ ቦታዎች ላይ መኪና ሲበላሽ የመጀመሪያ ስራ ወርዶ ዝቅ ብሎ ማየት አልሆነም የመጀመሪያ ስራ ወርዶ መሮጥ ነው ምክንያቱም እንደቆምክ አንድ ታጣቂ መጥቶ ሊያግትህ ወይም ሊገድልህ ይችላል ምን ተበላሸ ብለህ የምታየው አንድ ሚሊሻ ይዘህ ተመልሰህ መጥተህ ነው " ብለዋክ።
ማዕከላዊ ጎንደር ታች አርማጭሆ ከሶረቃ እስከ ሳንጃ፣ ፈረስ መግሪያ ፣ ' ኢትዮጵያ ካርታ ' የሚባለው አካባቢ ድረስ ለሹፌሮች አስቸጋሪ ሆኖ መቀጠሉን ገልጸው ሳንጃ እና አሽሬ ባለው የመንገድ ክፍል ከህዳር 25 እስከ አሁን ድረስ 5 ሹፌሬች እንደታገቱ ተናግረዋል።
ሃላፊው ፤ " ሰው የሹፌሮችን እገታ እና ግድያ አሁን በክልሉ ከሚታየው የጸጥታ ችግር ጋር ያያይዘዋል ነገር ግን እገታ በጠቀስናቸው አካባቢዎች 7 እና 8 ዓመት አልፎታል ሹፌርን ማገት የስራ ዘርፍ ሆኖ እየተኖረበት ነው " ሲሉ አማረዋል።
" በብዛት የሹፌሮች እገታ ያለበት አካባቢ ግጭት ያለበት አካባቢ አይደለም " ያሉት አመራሩ " ታገትን ተገደልን ብለን ስንናገር : ግጭት ወዳለበት አካባቢ እያሽከረከራቹ በመሆኑ ነው ' እየተባለ ይደበሰበሳል እንባላለንም ነገር ግን ይህ ለወንበዴ ሽፋን መስጠት ነው " ብለዋል።
በመተማ እና ጎንደር መሃል ቦና ፣ መቃ እና ግንታ አካባቢ አንድ ሹፌር እስከ 40 እና 50 ሺ ብር እንዲከፍል እንደሚገደድ አንስተው በ05/04/17 ሳይከፍሉ ያለፉ ሹፌር እና ረዳት በዚሁ አካባቢ መገደላቸውን አስታውሰዋል።
ለምንድነው የምትሰበስቡት ? ስንልም " ከምናግታቹ ብለን ነው " የሚል መልስ ይሰጠናል ብለዋል።
እገታ የሚፈጸምባቸው አካባቢዎች የፀጥታ ኃይል ካምፕ ያለበት ቢሆንም ለሹፌር ጥበቃ የሚያደርግ ሆነ ወንበዴዎችን የሚያጸዳ ሃይል እንደሌለ ተናግረዋል።
በዚህ ምክንያት በሳንጃ ሶረቃ መንገድ 2 ሺህ ብር በመክፈል በአጃቢ ሚሊሻ ለመንቀሳቀስ መገደዳቸውን ጠቅሰዋል።
በዚህ ጉዳይ ላይ የአካባቢውን የጸጥታ አመራሮች ምላሽ እንዳገኘን የምናካትት ይሆናል።
#TikvahEthiopiaFamilyAA
@tikvahethiopia